“እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደሥራቸው አታድርጉ” /ማቴ 23፥3/

የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 23 ሙሉውን ስንመለከት ጸሐፍት ፈሪሳውያን በስፋትና በተገቢ የተወቀሱበት ክፍል ሆኖ እናገኘዋለን፤ ወቃሹም ደግሞ ሁሉን የሚመረምር፣ ማን ምን እንደሆነ የሚያውቅ፣ እንደሰዎች፣ በሰዎች ንግግር የማሳመር ችሎታ የማይታለልና ልብና ኩላሊታችንን መርምሮ የሚያውቅ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ጸሐፍት ፈሪሳውያን እዩን እዩን የሚሉ ግብዞች፣ በጸሎት አሳበው የመበለቶችን ቤት የሚበሉ፣ እውነተኞችን የሚያሳድዱ፣ በሙሴ ወንበር ላይ ተቀምጠው ትክክለኛውን ነገር ለማስመሰል የሚናገሩ ግን ደግሞ በፍጹም  የማያደርጉት ናቸው፡፡ እነዚህ ጠባያትና ግብሮቻቸው ናቸው በፈጣሪያቸው እንዲወቀሱ ያደረጋቸው፡፡ በተለይ ተቀባይነት እንዲያገኙ በእርሱ ስምና በቃሉ እንዲሁም በሚለብሱት የአገልግሎት ልብስ  ላያቸውን ያሳመሩ ውስጣቸው ግን ርኩሰትን የተሞሉ መሆናቸውን ሲገልጽ፡- “እናንት ግብዞች ጸሐፊዎችና ፈሪሳውያን፣ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን ዐጥንት፣ ርኩሰትም ሁሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ ወዮላችሁ፡፡” ይላቸዋል፡፡ /ማቴ 23፥27/ ከዚህ የምንረዳው ጌታችን ያወገዛቸው ብቻ ሳይሆን በዚህ ተግባራቸው ወደፊት የሚገጥማቸው ነገር አስፈሪ መሆኑን ነው፡፡ በዚሁ ምዕራፍ ላይ ቁጥር 13 እና ቁጥር 15ን  በቅደም ተከተል ስናይ መንግሥተሰማያት ስለማይገቡና ስለማያስገቡ፣ ምእመናንን ከእነሱ ይልቅ ሁለት እጅ እጥፍ የገሃነም ልጆች ስለሚያደርጉና በጸሎት እያመካኙ የመበለቶችን ቤት ስለሚበሉ “ወዮላችሁ!” በማለት ስላደረጉት የሚጠብቃቸውን ቅጣት አመልክቷቸዋል፡፡ በቁጥር 14 ላይም “የባሰ ፍርድ ትቀበላላችሁ፡፡” ይላቸዋል፡፡

በዚሁ የመጸሐፍ ቅዱስ ክፍል ከቁጥር 1 ጀምረን ስናነብ እንደምናገኘው፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጸሐፍት ፈሪሳውያንን ጉዳይ ሲነግር የነበረው ለሕዝቡና ለደቀመዛሙርቱ ነበር፡፡ “በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ለሕዝቡና ለደቀመዛሙርቱ እንዲህ ብሎ ነገራቸው፡-ጸሐፊዎችና ፈሪሳውያን በሙሴ ወንበር ተቀምጠዋል፡፡ ስለዚህ ያዘዟችሁን ሁሉ አድርጉ፣ ጠብቁትም፤ ነገር ግን እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደሥራቸው አታድርጉ፡፡” /ማቴ 23፥1-3/ ያኔ በዚያን ጊዜ የተናገረው፣ ዛሬ በዚህን ጊዜም እንደሚሠራ ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ዛሬም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ ስለ ጸሐፍት ፈሪሳውያን መለያ ጠባያት መግለጹና እነሱን ማውገዙ ብሎም ወደፊት እየጠበቃቸው ስላለው መከራ መናገሩ በየዘመኑ ለሚነሡ ውሉደ ጸሐፍት ፈሪሳውያንም አጥብቆ ያገለግላል፡፡ በዘመናችን የጸሐፍት ፈሪሳውያንን ጠባያት የያዙ የሉምን? በርካቶች አሉ፡፡ ጌታችን እንደገለጻቸው በግብዝነት፣ በአስመሳይነትና በንዋይ ወዳድነታቸው የተዋጣላቸው ሲሆን፣ በተለይም በቃሉ እያታለሉ የሚሠሩት ያልተገባ ተግባር፣ ምንም እንኳን ውስጣቸው ባዶ ሆኖ ዛሬ ሁሉ የሞላላቸው ቢመስሉም፣ በእውነት ለንስሐ የተሰጣቸው ጊዜ ሲጠናቅ ፍጻሜያቸውን አለማሰብ ነው፡፡

ከላይ በርዕሱ ላይ እንደተመለከተው “እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደሥራቸው አታድርጉ” /ማቴ 23፥3/ ተብሎ እንደተነገረን፣ ዛሬ ጹሙ የሚሉ ግን በተገቢው ሁኔታ የማይጾሙ፣ ጸልዩ የሚሉ ግን የማይጸልዩ፣ ስለምጽዋት ሲናገሩ የተመሰገኑ ግን የማይመጸውቱና መጽውቱ የሚሉትም ለቤተ እግዚአብሔር ሳይሆን ለኪሳቸው የሆነ፣ በሃይማኖት ጽኑ የሚሉ ግን ደግሞ እዛኛውም ቤት እያገለገሉ ደመወዝ የሚበሉ፣ መማለጃን መቀበል የገሃነም ልጅ ያደርጋል የሚሉ ግን እነርሱ በእጥፍ የገሃንም ልጆች የሆኑ በርካቶች አሉ፡፡ ጌታችን እንዳዘዘን፣ መጽውቱ ሲሉን መመጽወት ነው፤ አለመመጽወታቸውንና እጃቸውን ወደ እግዚአብሔር ገንዘብ ሲሰዱ ግን እንከላከላቸው ይሆናል እንጂ እጃችንን እንደእጃቸው ልናደርግ አይገባም፤ አንከተልምም፤ጹሙ ሲሉን መጾም ነው፤ አለመጾማቸውን አናይም ወይም በጠዋት ቡና መጠጣታቸውን አንከተልም፤ አታመንዝሩም ይሉናል፤ መልካም ነው፤ ይህን መልካም ምክር እንከተላለን፤ ጌታችን እንዳዘዘን፣ ሲያመነዝሩና ሲዳሩ አንከተላቸውም፤ በዚህም የነገሩንን እንጂ የሚያደርጉትን አንከተልምና በኃጢአታቸው  የሚመጣባቸውን ጣጣም አንቀበልም፡፡

ጌታችን በሥጋዌው ወራት በዚህ ምድር ሲመላለስ በነበረበት ጊዜ የነበሩት ጸሐፍት ፈሪሳውያን መልካም የሚናገሩና የሚናገሩትን ግን የማያደርጉ ነበሩ፡፡ ይህ ተግባራቸው ከግብዝነታቸው፣ ከገንዘብ ወዳድነታቸውና  በቃሉ ከመነገዳቸው ጋር የሚያስከትልባቸውን ቅጣት ጌታችን “ወዮላቸው!” ሲል ገልጾታል፡፡ ዛሬ  እንዲህ አይነቶቹ ጸሐፍት በብዙ መገኘታቸውና በየቦታው የሚሠሩት የክፋት ሥራ እጅግ የሚደንቅ ሲሆን፣ ከዚህ በላይ የሚያስደንቀው ደግሞ በንግግርም በተግባርም የሌሉበት መሰሎቻቸው መፈልፈላቸው ነው፡፡ እርግጥ ነው ጥሩውን እየተናገሩ አለማድረግም ሆነ ክፋትንና ሰውን ሚያሳስቱ ነገሮችን እየተናገሩ መልካሙን አለመናገርና አለማድረግ አንድ ቢሆኑም፣ መልካም ተናጋሪዎች ግን ደግሞ የተናገሩትን የማይፈጽሙጹ ወዮላቸው ከተባሉ ክፉ ተናጋሪዎችና ክፉ አድራጊዎች ምን ይባሉ ይሆን? የሚናገሩት መልካም፣ የሚተገብሩት ግን ሌላ የሆኑትን ጌታችን እንዳደረገው በየወቅቱ ባለመገሰፃችንና ባለማረማችን ምናልባትም ማውገዝ ሲገባን ባለማውገዛችን ቁጥራቸውን ከመጨመራችን በላይ ከነርሱ የከፉና ንግግራቸው ጭምር መልካም ያልሆነ ከሃይማኖት ወደ ጥርጥር ብሎም ወደ ክህደት የሚወስዱ ከምግባርም የሚያስወጡትን አፍርተናል፡፡ ዛሬ ግን ከጌታችን እንደተማርነው፣ መልካሙን እየተናገሩ ክፉ ሚያደርጉትንም ሆነ፣ ሰውን ማፈር፣ እግዚአብሔርን መፍራት የሌላቸውን ያለምንም ፍርሃት ልንቃወማቸው፣ ልናርማቸው ብሎም ተገቢውን መረጃ ይዘን ልናጋልጣቸው ይገባል፡፡ እስከመቼ እንታገሳቸዋለን? እንደእውነቱ ከሆነ ለእነርሱም የሚሻላቸው ባንታገሳቸው ሲሆን፣ የእኛ ትእግስት (ምናልባትም በትእግስት ስም ፍራቻ ይዞን ይሆናል) የተሰጣቸውን የንስሐ ጊዜ በከንቱ እንዲያሳልፉና የእግዚአብሔርን ቸርነት እንዲሳለቁበት እያደረገ በመሆኑ ለምን ዝም እንዳልናቸው ራሳችንን ልንጠይቅ ይገባል፡፡ እነዚህ ወገኖች እያሳዩ ባሉት አስመሳይነት፣ ሙሰኝነትና ሌላም ሌላም ፈሪሳዊ ጠባያት የሚያገኛቸው ቅጣት “የባሰ ፍርድ ትቀበላላችሁ” /ማቴ 23፥14/ በሚል በጌታችን የተነገረ መሆኑን ስናነብ የወደፊቱ የባሰ ይሆናል እንጂ አሁን እየተቀጡ አይደለም ማለት አይደለም፡፡ ዛሬ  በአገልግሎት ልብስና በማይተገብሩት የእግዚአብሔር ቃል ተከልለው፣ ከገንዘብ ወዳድነት የራቁ በመምሰል ቤተክርስቲያንን የሚዘርፉ፣ ሃይማኖተኞች መስለው በዐውደ-ምሕረቱና እስከመቅደሱም ዘልቀው ሃይማኖትን ለማጥፋት የተሰገሰጉ ሁሉ እየተቀጡ መሆኑን ከማንም በላይ ራሳቸው ያውቁታል፡፡ እነዚህ ዕድለኞች ሆነው የንስሐ ጊዜ ያገኙ አስመሳዮች ከሕሊና ቅጣት ባሻገር በደዌ ሥጋ ጭምር እየተጠቀጡ ነው፤ በቤተሰቦቻቸው ላይ ጭምር መቅሰፍት እየተቀበሉ ነው፤ አትዝረፉ፣ መማለጃ አትቀበሉ እያሉ በንግግር የሚጠብቁት፣ በተግባር ግን የሚዘርፉት የቤተክርስቲያን ገንዘብ አዕምሯቸውን እንዲስቱ እያደረጋቸውና መጥፊያቸው እየሆነ ነው፤ ከዛሬ ነገ ተነቃብኝ እያሉ የሚኖሩት ቃየናዊ ሕይወትም  እያሰቃያቸው ይገኛል፡፡ ይህ እየሆነባቸው ነው እንግዲህ ጌታችን “የባሰ ፍርድ ትቀበላላችሁ” የሚላቸው፡፡ ከዚህ የከፋው ፍርድ እንዴት አስደንጋጭና አስፈሪ ይሆን? ሊያውም በፍጡር ሳይሆን በፈጣሪ የተነገረ! አዎ ንስሐ የማይገቡ፣ መሐሪው አምላካችን ብዙ ዝም ሲል ቸርነቱ ላይ የሚያላግጡትን ከዚህ የባሰ ፍርድ ትቀበላላችሁ ማለቱ ካልተመለሱ ገና በስጋቸው ብዙ እንደሚቀጡና በተለይም ደግሞ በነፍሳቸው የሚጠብቃቸውን ሲያሳያቸው ነው፡፡ Continue reading

መንፈሳዊነት ምንድን ነው?

ለመሆኑ መንፈሳዊነት ምንድን ነው? ረዥም ቀሚስ መልበስ ነው? ፀጉርን በአሮጌ ሻሽ መሸፈን ነው? ገላን ያለመታጠብ ነው? አንገትን መድፋት ብቻ ነው? ቀስ ብሎ መናገር ነው? ኋላ ቀርነት ነው? አይመስለኝም፡፡ ቴሌቭዥን አለማየት፣ኢሜይል አለመጠቀም ነው? ከጸሎት መጻሕፍት በቀር ሌላ ነገር አለማንበብ ነው? መንፈሳዊነትኮ በመንፈስ ቅዱስ መመራት ነው፡፡ ራስን ማሸነፍ ነው፡፡ አእምሮን እና ልቡናን ቀና እና ሰላማዊ ማድረግ ነው፡፡ ለመሆኑ የውስጡ መንፈሳዊነት አይደለም እንዴ ወደላይ መገለጥ ያለበት፡፡ ስለ ሐዋርያት ስንናገርኮ የነፍሳቸው ቅድስና ለሥጋቸው፣ የሥጋቸው ቅድስና ለልብሳቸው፣ የልብሳቸው ቅድስና ደግሞ ለጥላቸው ተረፈ ነው የምንለው፡፡ መንፈሳዊነቱ ከውስጥ ወደ ውጭ እንጂ ከውጭ ወደ ውስጥ አልነበረም፡፡ አንዳንድ ጊዜ “መንፈሳዊነት” ከ “መንፈሳይነት” ጋር እየተመሳሰለ የምንቸገር ይመስለኛል፡፡ ዲያቆን ኤፍሬም እሸቴ ነው ይህችን ቃል ያመጣት፡፡ ከሁለት ቃላት “መንፈሳዊ” እና «መሳይ» ከሚሉ ቃላት ቆራርጦ መንፈሳይ” የሚል ቃል ፈጠረ፡፡ ትርጉሙም መንፈሳዊ መሳይ” ማለት ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች መንፈሳውያን ይመስላሉ እንጂ አይደሉም፡፡
አባ ኤፍሬም ሶርያዊ ባስልዮስን ለማየት በሄደ ጊዜ ስለ ክብረ ወንጌል ሲል ከላዩ የወርቅ ልብስ ለብሶ ፣ የወርቅ ወንበር ዘርግቶ፣ የወርቅ ጫማ ተጫምቶ በጉባኤው ላይ ባየው ጊዜ «ደገኛ መምህር የተባለው ባስልዮስ ይኼ ነውን?» ብሎ ነበር፡፡ በኋላ ግን ተአምራቱን አይቶ አድንቆታል፡፡ አንዳንድ ጊዜ የውጭ ገጽታ ውስጥን ሊገልጥም ላይገልጥም ይችላልና፡፡ ልክ ነው ክርስቲያናዊ አነጋገር፣ አለባበስ፣ አረማመድ፣ ገጽታ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ማለት መንፈሳዊነት ጅልነት፣ ከርፋፋነት፣ ኋላ ቀርነት ወይንም ደግሞ፣ ንጽሕናን አለመጠበቅ ማለት ግን አይደለም፡፡ በመንፈሳዊነታቸው የሚደነቁት የቤተ ክርስቲያን ከዋክብት እነ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙ፣ባስልዮስ ዘቂሳርያ በዘመኑ በነበረው የግሪክ ፍልስፍና እና ዕውቀት የበለጸጉ ነገር ግን ዕውቀታቸውን እናሥልጣኔያቸውን በወንጌል የቃኙ ነበሩ፡፡ብዙዎቻችን ከውስጥ ለሚመነጩ ትእግሥትን፣ ደግነትን፣ ታዛዥነትን፣ ትኅትናን፣ አርቆ ማሰብን፣ ኀዘኔታን፣ ፍቅርን፣ ትጋትን ለመሰሉ ነገሮች ትኩረት አንሰጥም፡፡ ከዚያ ይልቅ ተዋንያን ሊያደርጉት የሚችሉትን የውጭ ገጽታን ብቻ በማየት መመዘን እንመርጣለን። እውነተኛው መንፈሳዊነት ግን ከመንፈሳይነት መለየት አለበት፡፡ መንፈሳይ ሰዎች የራሳቸው መለያ ባሕርያት አሏቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች ከውስጣዊ መንፈሳዊነት ይልቅ ለውጫዊ ነገሮች ትልቅ ትኩረት ይሰጣሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ውስጣዊ ማንነታቸውን ለመሸፈን ሲሉ ሕግ ከሚፈቅደው በላይ ለውጫዊ ገጽታ ይጨነቃሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስለ የፀጉር አያያዝ የራስዋ ባህል አላት፡፡ እነርሱ ግን ፀጉር መታጠብን ኃጢአት ያደርጉታል፡፡ ክርስቲያኖች የሚለብሱት ልብስ ራሳቸውን የማያጋልጥ እንዲሆን ትመክራለች፡፡ እነርሱ ግን ልብስ ሁሉ መሬት ካልጠረገ ይላሉ፡፡ ያደፈ በመልበስ፣ የአእምሮ ችግር ያለባቸው ይመስል እጅግ ቀሰስ ብለው በመናገር፣ ሰው መሆናቸውን ረስተው ምንም ነገር እንደማይበሉ እና እንደማይጠጡ በማሳመን፣ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ በመልበስ፣ ሰንሰለት በመታጠቅ፣ ትልልቅ መቁጠርያ እጃቸው ላይ በመጠቅለል፡፡ ይበልጥ መንፈሳዊ ሆነው መታየት ይፈልጋሉ፡፡

ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው በዱርዬ እና በሴተኛ አዳሪዎች ዘንድ ያለውን ያህል ፈሪሃ እግዚአብሔር በአገልጋዮች ዘንድ የለም ይል ነበር፡፡ አንዳንዶች በአገልግሎት እየበረቱ ሲሄዱ ከመንፈሳዊነት ወደ መንፈሳይነት ስለሚለወጡ፡፡ጋሽ ግርማ ከበደ ከሚያስተምረው ነገር የማልረሳው ቃል አለ፡፡ ሰው የሚጠላውን ኃጢአት ደጋግሞ ይሠራዋል” ይላል፡፡ ለምንድን ነው ደጋግሞ ይሠራዋል ያለው? እኔ እንደ ተረዳሁት መጀመርያውኑ ይህ ሰው ውስጡ ያላመነበትን እና ሊያደርገው የማይፈልገውን ነገር ነው ለማስመሰል ሲል እያወራ ያለው፡፡ ስለዚህም በውስጡ ያንን የጠላውን ነገር ላለማድረግ መንፈሳዊ ተጋድሎ ስለማያደርግ ደጋግሞ ሲሠራው ይገኛል፡፡ እንዲያውም አንዳንዶች መንፈሳያን ስለ አንድሰው መንፈሳዊነት ደጋግመው በጥላቻ ወይንም በንቀት፣ ወይንም ደግሞ በመመጻደቅ የሚያወሩ ከሆነ ያንጊዜ አንዳች ነገር ተረዱ፡፡ ሳያስቡት እየተናገሩ ያሉት ስለ ራሳቸው ነው፡፡ መንፈሳውያን ሰዎች ስለሌሎች ውድቀት ሲያነሡ ከርኅራኄ እና ከኀዘኔታ ጋር ነው፡፡ የደስታ ስሜት አይሰማቸውም፡፡ እንደ ጀብዱም አይቆጥሩትም፡፡ ለዚህም ነው በቅዳሴ አትናቴዎስ ሊቁ ስለ አዳምና ሔዋን አንሥቶ እኛስ እናንተን ልንወቅሳችሁ አንችልም” በማለት የተናገረው፡፡ መንፈሳውያን ይነበባሉ፤መንፈሳያን ግን ይታያሉ፡፡ መንፈሳውያን ይቀመሳሉ፣ መንፈሳያን ግን ይላሳሉ፡፡ መንፈሳውያን ያዳምጣሉ፤ መንፈሳያን ግን ይለፈልፋሉ፡፡ መንፈሳውያን ያስተውላሉ፤ መንፈሳያን ግን ይቸኩላሉ፤ መንፈሳውያን ያጠግባሉ፣ መንፈሳያን ግን ያቁለጨልጫሉ፡፡ መንፈሳውያን ይመዝናሉ፤ መንፈሳያን ግን ያፍሳሉ፡፡ መንፈሳውያን ያርማሉ፤ መንፈሳያን ግን ይተቻሉ፡፡ መንፈሳውያን ጠላቶቻቸውን አንድ ሺ ዕድል ይሰጣሉ፤ መንፈሳያን ግን ወዳጆቻቸውን ጠላቶቻቸው ለማድረግ አንድ ሺ በር ይከፍታሉ፡፡ መንፈሳውያን ይጾማሉ፣ መንፈሳያን ይራባሉ፤ መንፈሳውያን ይጸልያሉ፣ መንፈሳያን ግን ይናገራሉ/ያነባሉ፡፡ መንፈሳውያን ሱባኤ ይይዛሉ፣ መንፈሳያን ግን ስለ ሱባኤያቸው ያወራሉ፡፡ መንፈሳውያን ይሰጣሉ፣ መንፈሳያን ግን ሲሰጡ ያሳያሉ፡፡ መንፈሳውያን ቃለ እግዚአብሔርን ያስተምራሉ፣ መንፈሳያን ግን በራሳቸው ቃላት ይጠበባሉ፤ መንፈሳውያን ወደ ውስጥ፣ መንፈሳያን ወደ ውጭ ያያሉ፡፡ መንፈሳውያን የነገን፣ መንፈሳያን የዛሬን ያያሉ፡፡ መንፈሳውያን ምክንያቱን፣ መንፈሳያን ድርጊቱን ያያሉ፡፡ መንፈሳውያን ራሳቸውን፣ መንፈሳያን ሌላውን ያያሉ፡፡

Continue reading

በጎ ያልሆኑ ተጽእኖዎች በክርስትናችን

በተደጋጋሚ ከሚያጋጥሙኝ ክስተቶች አንዱ ይህ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከምተዋወቀው አንድ ልጅ ጋር ቁጭ ብለን እየተጨዋወትን ነው፡፡ ልጁን የማውቀው ሰ/ት/ቤት ውስጥ ታታሪ አገልጋይ በነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ አሁን ከመንፈሳዊ አገልግሎቱ ራሱን አግልሏል፡፡ እንደድሮው ስለመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያወያየው ለአገልግሎት የሚጋብዘው፣ ሲደክም የሚያበረታው፣ ሲሰለች መንፈሱን የሚያድስለት፣ ጓደኛ የለውም፡፡

ከሚሳተፍባት አጥቢያ  ሰ/ት/ቤት መራቁን እንደ ትልቅ ምክንያት እያነሳ በተደጋጋሚ ነገረኝ ምክንያቱ አልተዋጠልኝም፤ የራቀው ከአንድ አካባቢ እንጂ ቤተ ክርስቲያንና ሰ/ት/ቤት አሁን ካለበት አካባቢ እንዳለ አውቃለው፤ ከተለያየን በኋላ ስለጉዳዩ በደንብ አሰብኩበት፡፡ ይህ ችግር የብዙ ሰዎች ችግር እንደሆነ በተደጋጋሚ እናያለን፤ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትን በጊዜና በቦታ የመገደብ፣ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትንና አገልግሎትን የማስኬድ ችግር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ይህም አንድ ነገር እንዳለ ያመላክተናል። ይህም ክርስትናችን የቆመበት መሠረት በነፋስና በጎርፍ ተጠራርጎ ለመውደቅ ቅርብ መሆኑን ነው። ለዚህ ነው ጥቃቅን ምክንያቶች ግዙፍ የሚመስለንን ግን ያልሆነውን ክርስትናችንን አደጋ ላይ የሚጥሉት የሁሉም ነገር መነሻ መሠረቱ ነውና፡፡ ክርስትናም የራሱ መሠረት አለው፡፡ እስኪ በተረጋጋ መንፈስ ክርስትናችን የተገነባበትን እንመርምር፡፡ በክርስቲያናዊ ሕይወታችን ውስጥ ልብ ልንላቸው የሚገቡ ነገር ግን እንደዋዛ የምናያቸውን ነጥቦችን እንደሚከተለው እንመለከታለን፡-

በሌሎች ጫንቃ ያረፈ ክርስትና ነው ያለዎት?

ሁሌም ልብ ልንለው ከሚገቡ ነጥቦች አንዱ ክርስትናችን ማንን ተስፋ እንዳደረገና በማንስ ላይ ተስፋውን እንደጣለ መረዳት ነው፡፡ የብዙዎቻችንን መንፈሳዊ ዐይን ሸፍኖ ዋናውን ነጥብ እንዳናይና የሚያደርጉ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ በአካባቢያዊና በአጥቢያ ላይ የተመሠረተ የአገልግሎተ ፍቅር፣ በማኅበራት ትክሻ ላይ የተንጠላጠለ ሱታፌ፣ ከጓደኝነትና ከመላመድ የመነጨ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ዋናውን የክርስትና ዓላማ  እንዳንረዳ ከሚያደርጉን መሰናክሎች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እነዚህ ነጥቦች ለክርስትናችን እንደ ግብዓት የሚታዩ እንጂ የአገልግሎታችንና የክርስቲያናዊ ሕይወታችን መሠረቶች ሊሆኑ አይገባም፡፡ ልብ ብሎ ራስን መመርመር የሚገባም ለዚሁ ነው፡፡
ግድግዳና ጣሪያ ብቻ ለቤት መሠረት ሊሆኑ እንደማይችሉ ሁሉ በሰው በማኅበር መሠባሰብ ላይ የተመሠረተ ክርስትናም ዘላቂነት የለውም፡፡ ብዙዎች ከሚያገለግሉበት አጥቢያ ሲርቁ፤ በክርስትና ከሚያውቋቸው ጓደኞቻቸው ሲለዩ ከቤተክርስቲን ለመራቅ ያስባሉ፡፡ ክርስትና እዚያና እዚህ ብቻ ያለ ይመስላቸዋል፤ ክርስቲያናዊ ሕይወት የእነ እገሌ ተሰጥዖ  ብቻ አድርገው ይወስዳሉ፤ ቀስ በቀስም ተስፋ የመቁረጥና የብቸኝነት ስሜት በልባችን ሰርጾ ይገባል፡፡ ከለመድነው አሰራርና አካሄድ የተለወጠ ነገር ባየን ቁጥር እየበረገግንና እየራቅን እንመጣለን። ስለዚህ በድሮው ክርስትናችን መቀጠል ይከብደናል፡፡ ዴማስ ከለመደው ከተማና ሁኔታ የተለየ ሁኔታ ስለገጠመው ነበር በተሰሎንቄ ተስቦ የቀረው /2ኛ ጢሞ/ ብዙዎች የተሰናከሉት የሰው ልጆችን ኑሮ በማየታቸውና ከለመዱት የአኗኗር ዘየ የተለየ ነገር ስለገጠማቸውና ስለተሸነፉለትም ነበር። /ኩፋ 6፥9 ዘፍ 6፥1/  የያዕቆብ ልጅ ዲናም ከክብር ያነሰችው የለመደችውን የአህዛብ አኗኗር መቋቋም አቅቷት ነበር፡፡ ዘፍ 34፥1 የብዙዎቻችንም ክርስትና እንዲሁ ለፈተና የተጋለጠ ነው፡፡ አካባቢን ከመለወጥ ይልቅ እኛው ተለውጠን ክርስትናችን ደብዛው የጠፋብን ብዙዎች ነን፡፡ የማኅበረ እስጢፋኖስ መበታተን ክርስትናን የበለጠ እንዲስፋፋ አደረገ እንጂ ክርስትናቸውን አላጠፋባቸውም፡፡ በጊዜና በቦታ ሳይወሰኑ አሐቲ የሆነችውን ቤተክርስቲያን ማገልገል የቤተክርስቲያንን የአገልግሎት ሁኔታ የመረዳትና የክርስትናንም ውል የመያዝ ምልክት ነው፡፡ ከመንፈሳዊ ሩጫችን ጎን ለጎን ልናስተውለውና ልንረዳው የሚገባን ቢኖር እያገለገልኩና እየሮጥኩ ያለሁት ከራሴ በሚመነጭ መንፈሳዊ ግፊት ነው ወይስ በስብሰባ ድምቀት ልምድ ስለሆነብኝ? ወይንም ከሰ/ት/ቤት ልጆች መራቅ ስላልፈለግሁ ነው የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ Continue reading

መንፈሳዊ ሕይወት

በመንፈሳዊ ሕይወት ለመኖር ከእኛ የሚጠበቁ ነገሮች ምንድን ናቸው? የሚል ጥያቄ በሕሊናችን መመላለሱ አይቀሬ ነው። ለጥያቄያችሁ መልስ ለማግኘትና በመንፈሳዊ ሕይወት ጸንተን ለመኖር የሚከተሉትን ትዕዛዞች ተግባራዊ እናድርጋቸው፡፡

ቃለ እግዚአብሔርን መማር

መንፈሳዊ ሕይወት ቀስ በቀስ የሚያድግ ስለሆነ በአንዴ ተነስቶ መንፈሳዊ ሰው መሆን አይቻልም። ያለንን መንፈሳዊ ጸጋም እስከመጨረሻው አጽንተን የምንጓዝ ምግበ ነፍስ የሆነውን ቃለ እግዚአብሔር  ስንሰማና ስንማር ነው።  ሰው መማሩን፣ መጠየቁን፣ የአባቶችን ምክር ካቆመ ለተለያዩ ፈተናዎች እየተጋለጠ መሄዱን ያሳያል። ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም /ማቴ 4፥4/  ተብሎ እንደተጻፈ መማር፣ ቅዱሳት መጽሐፍትን ማንበብ፣ አባቶችን መጠየቅ በእግዚአብሔር እንድንታመን፤ በቅዱሳን አማላጅነና ተራዳይነት አምነን እንድንጠቀም፤ የቤተክርስቲያናችንን ታሪክ፣ ሕግ፣ ሥርዐት፣ ዶግማና ቅኖና እንድናውቅ ያደርጋል።

ቅዱስ ጳውሎስ የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሳጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።” /2ጢሞ 3፥16/  እንዳለ ቅዱሳት መጽሕፍት ለመንፈሳዊ ሕይወት እጅግ አስፈላጊዎች ናቸው። በእርግጥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በቀላሉ ማግኘት ከባድ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ዛሬ የምንኖርባት ዓለም በቴክኖሎጂ ሰውን ከሰው ማገናኘት፣የምንፈልገውንም ነገር በፍጥነት  ለማገናኘት የምታስችልበት ደረጃ ላይ ደርሳለች። ስለዚህ ይህን የቴክኖሎጂ የመረጃ  መረብ ለመንፈሳዊ አገልግሎት በመጠቀም ለነፍሳችን የሚያስፈልጋትን ምግብ መመገብ እንችላለን። እዚህ ላይ ግን በጥንቃቄ ማወቅ የሚገባን ነገር ትክክለኛው የቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ የሚተላለፍበት ድረ ገጽ የቱ ነው የሚለው መሰመር አለበት። ብዙዎች በስሜ ይመጣሉ የሚለው የወንጌል ቃል ይፈጸም ዘንድ በርካቶች በቤተክርስቲያናችን ስም የጡመራ ድረ ገጽ ከፍተው ቅዱሳንን ሲሳደቡ፣ የብሉይና የሐዲስን ሕግ አሟልታና አስማምታ የያዘችውን ቤተክርስትያን ሲተቹ፣ ከዚህም አልፎ እመ አምላክ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያምን መግለጽ በሚከብድ መልኩ ሲጽፉና ሲናገሩ እናያለን እንሰማለን። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል ከእነዚህ ደግሞ  ራቅ” /2ጢሞ 4፥5/  ብሎ ለመንፈስ ልጁ ለጢሞቴዎስ እንዳስጠነቀቀው እኛም ከእነዚህ ርቀን የራሳችን የሆኑትን ድረ ገጽ ለይተን በመጠቀም መንፈሳዊ ሕይወታችንን ማሳደግ ይኖርብናል።

ትእዛዛተ እግዚአብሔርን መጠበቅ

አባቶቻችን ሃይማኖት ካለሥርዐት ዋጋ የለውም፤ ካለምግባር መንግሥተ ሰማያት ሊያስገባን አይችልም በማለት የእግዚአብሔርን ትእዛዝና ሕግ መፈፀምና መጠበቅ እንዳለብን በአጽንኦት ይነግሩናል። ምክንያቱም የእግዚአብሔር ሕግና ትዕዛዝ ሁሉን አሟልቶ የያዘ ነውና። በትእዛዛቱ ውስጥ ስለእግዚአብሔር ማንነትና ምንነት፣ መልካም ምግባር መፈፀም እንዳለብን እና የሃይማኖታችንን ሥርዐትና ሕግ እንረዳበታለን። ስለዚህ በመንፈሳዊ ሕይወት ለመኖርና መንፈሳዊ ሰው ለመሆን ትዕዛዙን መፈፀምና መጠበቅ ያስፈልጋል።

እግዚአብሔር እንዲህ ይላል የሚወደኝ ቢኖር ትእዛዜን ይጠብቅ” /ዮሐ 14፥15/ መቼም እግዚአብሔርን የማይወድ ማንም የለም እርሱን የምንወድ ከሆነ ደግሞ ትዕዛዙን መጠበቅ ነው። እግዚአብሔርም በእኔ የምታምኑ ከሆነ፣ ከወደዳችሁኝ፣ ከአከበራችሁኝ ሕግና ትዕዛዜን ጠብቁ ፈፅሙ በማለት ትዕዛዙን መጠበቅ እርሱን መውደዳችን የምንገልፅበት መንገድ መሆኑን ይነግረናል።“ትዕዛዜ በእርሱ ዘንድ ያለችሁ የሚጠብቃትም የሚወደኝ እርሱ ነው” /ዮሐ 14፡21/ በማለት 6ቱ ቃላተ ወንጌልን ማቴ 5፥21 እና 10ቱ ትዕዛዛተ ኦሪት ዘፀ 20፥1-17 ከጾምና ከጸሎት ጋር መፈጸም እንዳለብን ያስረዳናል።

ጾምና ጸሎት

ጸሎት ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር፤ እግዚአብሔርን ማመስገን፣ መለመን፣ መጠየቅ መማጸን ማለት ነው። እንዲሁም ሰው አሳቡን ለእግዚአብሔር የሚገልጥበት፣ እግዚአብሔር የሰውን ልመና ተቀብሎ ፍቃዱን የሚፈፅምበት ረቂቅ ምስጢር ነው። ጾምና ጸሎት ሁለቱ የማይለያዩ የእግዚአብሔር የበረከት ስጦታዎች ናቸው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌ በምድር በነበረበት ጊዜ ከፈፀማቸው አበይት ተግባራት መካከል ጾምና ጸሎት ይገኙበታል። እርሱ የዲያብሎስን ፈተና በጾምና በጸሎት ድል እንደምንነሳው በገዳመ ቆሮንቶስ ለ40 ቀንና ለ40 ሌሊት ጾሞና ጸልዮ አሳይቶናል። ማቴ 4፥1 ስለጾም ኢትዮጵያዊ ቅዱስ ያሬድ ንጹም ጾም ወናፈቅር ቢጸነ፣ ወንትፋቀር በበይናቲነ፣ ዓይን ይጹም እምርእየ ሕሱም፣ ዕዝን ይጹም እምሰሚዓ ሕሱም፣  ልሳንኒ ይጹም እምተናግሮ ሕሱም ትርጉም ጾምን እንጹም፣ ባልንጀራችንን እንውደድ እርስ በርሳችን እንዋደድ፣ ዓይን ክፉ ከማየት ጀሮ ክፉ ከመስማት፣ አንደበትም ክፉ ከመናገር ይጹም  በማለት እንዴት መጾም እንዳለብን በሚገባ ገልጾልናል።  Continue reading

ኒቆዲሞስ

ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ የምስራቹን ቃል ሲያውጅ እስራኤላውያን የተቀበሉት በተደበላለቀ ስሜት ነበር፡፡ በአንድ በኩል ሕዝቡ ለብዙ ዘመናት በባርነት ሲገዛ ስለነበር ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲህ ይፈልጋሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሕዝቡ ለብዙ ዘመናት በባርነት ቀንበር ስለደከመ ተስፋ በመቁረጥ ተዳክሞ ነበር፡፡ መሲህ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ ሰራዊት አስከትሎ ነው ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው ክርስቶስን መሲህ ነኝ ብሎ ሲመጣ ለመቀበል ፈቃደኞች አልነበሩም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ጦር ሳይዝ ሰራዊት ሳያስከትል እንዲሁ ባዶ እጁን አርነት ላወጣችሁ መጥቻለሁ እያለ ደጋግሞ ተናግሯልና ነው፡፡ ምንም እንኳ አብዛኛው እስራኤላዊ የክርስቶስን መሲህነት ቢጠራጠርና ባይቀበለውም፣ በፍጹም እምነት እስከ መጨረሻው የተከተሉትም ነበሩ፡፡ ለዚህም ትልቅ ማሳያ የሚሆነን ከፈሪሳውያን ወገን የሆነ ኒቆዲሞስ የተባለ አይሁዳዊ ነው፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲያንም ይህን ታላቅ ሰው ለማዘከር የዐቢይን ጾም ሰባተኛ እሁድ በእርሱ ስም ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ተከታዮቿ ምዕመናንም የእርሱን አሰረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች ታስተምራለችም፡፡

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ነው 

የእስራኤላዊያን ለብዙ ዘመን በባርነት መኖር የሕዝቡን የአኗኗር ሁኔታ ቀይሮታል፡፡በግዞት ጊዜ ከአሕዛብ የቀሰሟቸው አጉል ትምህርቶች በእምነትም በአስተሳሰብም እጅግ እንዲለያዩና እንዲራራቁ ምክንያት ሆኗል፡፡ አይሁዳዊ ሳምራዊ፤ ከአይሁድም ሰዱቃዊ፣ ፈሪሳዊ፣ ጸሐፍት፣ ኤሴያዊ ብለው እንዲከፋፈሉ ከዚህም እጅግ ወርደው ገሊላዊ ናዝራዊ እንዲባባሉ ያበቃቸው ከአህዛብ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ፈር ባለማስያዛቸው ነበር፡፡ ፈሪሳዊያን ደግሞ ሕግን በማጥበቅ ሕዝቡን የሚያስመርሩ ቀሚሳቸውን በማስረዘም እነሱ የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑ ራሳቸውን ከሌሎች በላይ ከፍ ከፍ የሚያደርጉ አባታችን አብርሐም እያሉ የሚመጻደቁ የአባታቸው የአብርሐምን ስራ ግን የማይሰሩ ክፍሎች ናቸው /ዮሐ 8፥39/፡፡ ታዲያ ኒቆዲሞስ ምንም እንኳ ከፈሪሳዊያን ወገን ቢሆንም ራሱን ከዚህ ሕዝብ ለይቶ ክርስቶስን ፍለጋ  በፍጹም ልቡ የመጣ ፈሪሳዊ ነው፡፡ ቀድሞ አባታችን አብርሃምን ከቤተሰብህ ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ ያለው አምላክ ኒቆዲሞስን ከፈሪሳዊያን ለይቶ ጠራው፡፡ /ዘፍ 12/

ኒቆዲሞስ  የአይሁድ አለቃ ነው

ሮማውያን ሕዝቡን የሚያሥተዳድሩት ከላይ ያለውን ዋና ሥልጣን ተቆናጠው ታች ያለውን ሕዝብ ደግሞ ባህላቸውን በሚያውቅ ቋንቋቸውን በሚጠነቅቅ አይሁዳዊ ምስለኔ ነው፡፡ አውሮፓውያንም አፍሪካን ለመቀራመት የተጠቀሙበት ስልት ይህን ዓይነት ነበር፡፡ ኒቆዲሞስም ምንም እንኳ ፈሪሳዊ ቢሆን አለቃ እንዲሆን በሮማውያን የተሾመ ባለሥልጣን ነው፡፡

አንዳንዴ ሳያውቁ አወቅን ሳይማሩ እናስተምር የሚሉ ደፋር መምህራን አይጠፉም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ከዚህ በተለየ አለቅነትን ከመምህርነት መምህርነትን ከምሁርነት አስተባብሮ የያዘ ዕውቀትን ከትህትና ምሁርነትን ከደፋርነት አንድ አድርጎ የያዘ ሰው ነበር፡፡ የኦሪት ምሁር መሆኑን የሚጠቁመን ደግሞ ከካህናት አለቆች ጋር ያደረገውን ክርክር ባስታወስን ጊዜ ነው፡፡

ለምስጢረ ጥምቀት መገለጥ ምክንያት ሆነ 

የአይሁድ የፋሲካ በዓል እየቀረበ ሲመጣ ክርስቶስ ቀኑ እንደደረሰ ለሐዋርያቱ ተናግሮ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ እንደ ሰውነቱ ሰለቸኝ ደከመኝ ሳይል ሕዝቡን ቀንና ሌሊት በትምህርትና በተዐምራት ያገለግል ነበር፡፡ በዚህ ሰዐት ነው ኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ ወደ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው፡፡ በፊቱ ቀርቦም “መምህር ሆይ” ብሎ የእርሱን አላዋቂነት የክርስቶስን ማእምረ ኅቡዐትነት (የተሰወረን አዋቂነት) መሰከረ፡፡ ጌታችንም አመጣጡ ከልብ መሆኑን አውቆ ምሥጢረ ጥምቀትን (ዳግም ውልደትን) ገለጸለት፡፡ ምስጢሩ የኦሪት ምሁር ለነበረው ኒቆዲሞስ ለጆሮ የከበደ ለመቀበል የሚቸግር ሆነበት፡፡ የከበደውን የሚያቀል የጠበበውን የሚያሰፋ አምላክ ምሥጢሩ ለኒቆዲሞስ  እንደከበደው ስለተረዳ ቀለል አደረገለት፡፡ ዳግም ውልደት ከእናት ማኅፀን ሳይሆን ከውሃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደሆነ አብራራለት፡፡

አዋቂ ነን የሚሉትን አሳፈራቸው 

ወቅቱ የአይሁድ የፋሲካ በዓል የቀረበበት ጻፎችና የካህናት አለቆች ጌታን ለመያዝ፣ እንደሙሴም ህግ ሊያስፈርዱበት የቋመጡበት ጊዜ ነበር፡፡ የሙሴ ፈጣሪ መሆኑን መቸ አወቁና? የካህናት አለቆች ተሰብስበው ክርስቶስን ለመያዝ በሚመካከሩ ጊዜ ከሙሴ መጽሐፍ ሕግ ጠቅሶ ሊቃውንተ ኦሪትን አፍ ያስያዛቸው እሱ ነበር፡፡በዚህም የተነሳ ሳይስማሙ ወደየቤታቸው እንዲበታተኑ ምክንያት የሆነ ታላቅ ሰው ነው፡፡ Continue reading

የዓምደ ሃይማኖት በዓለ ልደት

በመንበረ መንግሥት (ግቢ) ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ት/ቤት የተመሠረተበትን 52ኛ ዓመት የልደት መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. በታላቅ መንፈሳዊ ሥነሥርዐት እንደሚያከብር የበዓል አዘጋጅ ኮሚቴው ከላከልን መግለጫ ለማወቅ ችለናል፡፡ የበዓል አዘጋጅ ኮሚቴው መግለጫ እንደሚያመለክተው ዝግጅቱ ሁለት ቀናትን ታሳቢ አድርጎ ተሰናድቷል፡፡

St.Gebreal

የዋዜማ መርሐ ግብር

የዋዜማው መርሐ ግብር የሚከበረው ቅዳሜ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡00- 1፡30 ሲሆን፤ የ3፡30 ቆይታ እንዳለውና የሚከተሉትን ዝግጅቶች እንደያዘ ተነግሮናል፡፡

  • የመክፈቻ ጸሎት በገዳሙ ካህናት
  • መዝሙር በሕፃናት
  • ትምህርት ሰ/ት/ቤቱ ባፈራቸው መምህራን
  • ልዩ ዝግጅት በሕፃናት
  • ወረብ በሰ/ት/ቤቱ መዘምራን
  • መዝሙር በአባላቱ
  • የመዝጊያ ጸሎት

Cover copy

የበዓሉ ዝግጅት

የሰንበት ት/ቤቱ 52ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል የሚጀምረው እሑድ መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00-1፡30 ነው፡፡ የመርሐ ግብሩ ይዘትም፡-

  • የመክፈቻ ጸሎት በገዳሙ ካህናት
  • መዝሙር በሕፃናት
  • ሪፖርት በሰ/ት/ቤቱ ጸሐፊ
  • መዝሙር በተጋባዥ ዘማርያን
  • ትምህርት ሰ/ት/ቤቱ ባፈራቸው መምህራን
  • ግጥም እና መነባነብ በሥነ ጥበብ ክፍል
  • ወረብ በሰ/ት/ቤቱ መዘምራን
  • ሽልማት በትምህርታቸው ብልጫ ላመጡ አባላት
  • መዝሙር በዐውደ ምሕረት በሰ/ት/ቤቱ ነባር አባላት
  • የመዝጊያ ጸሎት በገዳሙ አስተዳዳሪ

wereb

በትምህርተ ሃይማኖት ኮትኩታ በሥነ ምግባር አንፃ ያሳደገቻችሁ ዓምደ ሃይማኖት ሰንበት ት/ቤታችሁ 52ኛ ዓመት የልደት በዓሏ ለማክበር ዝግጅቷን አጠናቃ በእቅፏ ያደጉ ልጆቿ እንዲገኙላት መንፈሳዊ ጥሪዋን ታስተላልፋለች ብለውናል አዘጋጅ ኮሚቴዎቿ! Continue reading

የአዲስ ዓመት ስያሜ

ኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ አሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

ዘመን መለወጫ

ዘመን መለወጫ መስከረም ወር የሆነበት ምክንያት “ብርሃናት /ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ 364 ቀናት ይሆናል፡፡ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ /ሄኖክ.26፥44/ ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድሱ /ሰ.ኤር.5፥21/ እንዲል፡፡

images-1

በዘመነ ኖኅ ዓለምን ንፍር ውኃ አጥለቅልቆት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ውኃው የጎደለበት በመሆኑ /ኩፋሌ 7፥1/ በመጀመሪያው ወር መባቻም ምድር ታየች” እንዲል፡፡

ዕንቁጣጣሽ

ዕንቁጣጣሽ የተባለበት ምክንያት አንደኛ “ዕንቁ – ዕፅ አመጣሽ” ብሎ የአበባውን መፈንዳት ያመለክታል፡፡ ሁለተኛ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በእጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኀ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሦስተኛው /1ነገ.10፥1-10/ ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሣባ /አዜብ የንጉሡን ጥበብ ከመስማት ማየትን መርጣ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ከብዙ ሠራዊቶቿ ጋር የእጅ መንሻ በመያዝ ሄደች፡፡ ንጉሡም በደስታ ተቀብሎ እርሱም “እንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንሽ” በማለት አራት አይነት ቀለም የሚታይበት በቀንና በሌሊት የምታበራ ቀለበት ሰጥቷታል፡፡ ወሩም ወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜ ወጥቷል፡፡

images-2

 ቅዱስ ዮሐንስ

ሦስተኛው የአዲስ ዘመን ስያሜ ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ /ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1-3/ መጽሐፈ ስንክሳር “የመስከረም ወር የተባረከ ነው፡፡ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል 12 ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ቀኑ እየጎደለ ይሄዳል” እንዲል፡፡

images-3 Continue reading

ጾመ ሐዋርያት

ጾም ማለት ሰውነት ከሚፈልጋቸው ነገር ሁሉ መከልከል ማለት ነው፡፡ ወይም ለሥጋ የሚመቸውን ነገር መተው ማለት ነው፡፡ ሃይማኖት ባለበት ሁሉ ጾም አለ ጾም ከሃይማኖት ጋር ዘለዓለማዊ ዝምድና አለው፡፡ ይልቁንም በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ ነበረው፡
የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር ጋር በሚገናኙበት ወራት እህል ውኃ ለአፋቸው አይገባም ነበር፡፡
/ዘዳ 34፥28/ በኃጢአታቸው ብዛት የመጣባቸው መዓት የሚመልሰው ቁጣውም የሚበረደው ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር፡፡ /ዮና 3፥5-10/፡
በአዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይሆን ራሱ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕል ሥጋዌው መጀመሪያ አድርጎ የሠራው ሕግ ነው፡፡ /ማቴ 4፥21/ ጌታችን በሦስት በፍቅረ ንዋይና በትዕቢት የሚመጣበትን ጠላት ዲያብሎስ በጾም ድል እንድምንነሣው አሳየን፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን በቁራኝነት አብሮ የሚኖር ጠላት ሰይጣንን በጾም የሚወገድ መሆኑን መድኃኒታችን ተናግሯል /ማቴ 17፥21/፡
ስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስት የሚሾሙትም በጾምና በጸሎት ነበር፡፡ /የሐዋ13፥3፤4፥25/ እነ ቅዱስ ቆርኔሌዎስ ያላሰቡትን ክብር ያገኙት በጾማና በጸሎት ፈጣሪያቸው ማልደው ነው /የሐዋ 10፥20/

ጾም እንኳን የጠበቅነውንና ያሰብነውን ቀርቶ ያላሰብነውንና ያልጠበቅነውን ፈጽሞም የማይገባንን ጸጋና ክብር የሚያሰጥ ነው፡ በሐዋርያት መሠረት ላይ የተመሠረተች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የጾም ሕግና ሥርዓት አላት እነዚህም የፈቃድና የአዋጅ አጽዋማት ይባላሉ፡፡ ከሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዱ የሐዋርያት (የሰኔ) ፆም ነው፡፡

ይህም ጾም በሕዝብ ዘንድ የወታደር ጾም ይባላል፡፡ ለስብከተ ወንጌል ዘመቻ የተዘጋጀ በጾሙት ተምሣሌት በድሮ ዘመን ወታደሮች ለዘመቻ ሲነሱ ወይም ከዘመቻ ሲመለሱ በተሳተ በተገጸፈ ይቅር በለን በማለት ይጾሙት ነበር፡፡ ይህም ጾምየሚፈሰክበት ከሐምሌ 5 የማይለቅ ቢሆንም የሚጀመርበት ግን የተወሰነ ቀን የለውም በዚህም ምክንያት የጾሙ ዕለት ቁጥር ከፍና ዝቅ ይላል አንዳንድ ጊዜ ከአርባ ይበልጣል አንዳንድ ጊዜ ከ30 ያንሣል የ2008 ዓ.ም. ጾም ሰኔ 13 ገብቶ ለሦስት ሳምንት ይጾማል፡፡

images

ሐዋርያት መቼ ጾሙ?

ቅዱሳን ሐዋርያት የአምላካቸውን የመምህሮቸዋል አርአያ ተከትለው እርሱ ወደ ማዳን ሥራው /ሕሙማነ ሥጋን በተዓምህራት/ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርት ከማዳን አስቀድሞ የሥራውን መጀመሪያ በገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ 40 ቀን 40 ሌሊት እንደ ጾመና እንደጸለየ ሁሉ ቅዱሳን ሐዋርያትም አብነቱን ተከትለው ጾመዋል፡፡ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ዓለምን ዕጣ ተጣጥለው (ተከፈፍለው) ዞረው ከማስተማራቸው አስቀድመው የሥራቸው መጀመሪያን ጾምን አድርገዋል፡፡

ሐዋርያትም ይህንን ጾም እንደሚጾሙ ጌታችን አስቀድሞ የዮሐንስ ደቀመዛሙርት ወደ እርሱ ቀርበው በጠየቁት ጊዜ ተናግሮ ነበር፡፡ እኛና ፈሪሳውያን ብዙ ጊዜ የምንጦመው ደቀመዛሙርትህ ግን የማይጦሙት ስለምንድን ነው? አሉት ጌታችን ኢየሱስም እንዲህ አላቸው ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉ? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወስድበት ወራት ይመጣል በዚያን ጊዜም ይጦማሉ” /ማቴ 9፥15-16/፡፡

የሰኔ ጾም የቄስ ብቻ ነውን?

ይህ ጥያቄ ብዙ ሰዎች የሚነሣ ጥያቄ ነው ብዙ ምእመናን የሰኔን ጾም አይጾሙም ለመጾም የሚፈልጉትንም ሰዎች የቄስ ነው እያሉ ሲነቅፉ ይታያሉ ነገር ግን ይህ ጾም ከሰባቱ የአዋጅ ጾም አንዱ ነው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታቸንን ምሣሌ አድርገው የጾሙት እኛም እነርሱን አርአያ አድርገነው ልንጾመው የሚገባ የበረከት ጾም ነው፡፡ በዘመናችን ያሉ አንዳንድ “ክርስቲያኖች ነን” ባዮች “ከመጾም ተቆጥበው ቀሳውስት ብቻ የሚጾሙት ነው!” ይላሉ ለራስ የከበደን ነገር በሌላው ላይ መጫን ተገቢ አይደለም ካላወቁ ለማወቅ መማር ዐውቆ ከማጥፍት መቆጠብ ተገቢ መሆኑን መዘንጋት አይገባም

እኛ ይህን ጾም የምንጾመው የሐዋርያትን በረከት ለመካፈል፣ እነርሱ ድል ያደረጉትን ዓለም እንድናሸንፈው አምላካችንን ለመማጸን በመሆኑ ይህንን ዲያብሎስን ድል ማድረጊያ መሣሪያ አንጣለው ጾሙም ለመላው ክርስቲያን የተሰጠ እንጂ የቀሳውስት ብቻ አይደለም ለቄስና ለምእመናን ተብሎ በክህነት ደረጃ የተለየ ጾምም የለም፡፡

እንዴትና ከምን እንጹም?

የጾም ሃይማኖታዊ ትርጉም ፈጣሪን መለመኛ ከኃጢአት ቁራኛ መላቀቂያ መሣሪያ ስለሆነ በጾም ወራት ለአምሮት ለቅንጦት የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የሆኑ የአልኮል መጠጦች ሥጋና ቅቤ ወተትና እንቁላል ማራቅ ተገቢ ነው፡፡
ሥጋዊ ጉልበትን በጾም የማድከም ቅብአት ካላቸው ምግቦች መከልከልም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ አለው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙር ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ ሥጋዮም ቅቤ በማጣት ከሳ” ብሏል /108፥24/፡፡ ሠለስቱ ደቂቅና ነቢዩ ዳንኤልም የቤተ መንግሥቱን ሥጋና የጸሎት ምግብ ትተው በጥሬና በውኃ መቆየታቸው ተጽፏል /ት.ዳን 1፥8-21፣ት.ዳን10፥2/ ዋናው ነገር ጾም እንጂ መብል ወደ እግዚአብሔር አያቀረበንም ብንበላም የምናተርፈው ባንበላም የሚጎዳን ነገር የለም፡፡ /1ኛ ቆሮ8 ፥8/ ከአዳም ጀምሮ መብል ሲጥል እንጂ ሲያነሣ አላየንምና ጾሙን ከኃጢአት በመራቅ ለራስ ያስብነውን ለነዳያን በመስጠት፣ ጾም ከጸሎት ጋር ሲሆን ጸጋን እንደ ሐዋርያቱ ያሠጣልና በጸሎት በመትጋት በስግደት ወደ እግዚአብሔር በፍጹም ልብ በመመለስ ልንጾመው ይገባል፡፡ Continue reading

«የሚጐድለኝ ምንድር ነው»? /ማቴ ፲፱ ፥፳/

የጉድለት ነገር ሲነሣ ሁልጊዜ ትዝ የሚለን በኃላፊው ጠፊው ዓለም በሥጋ የሚጐድለን ብቻ ነው። ያማረ ቤት ፥ አዲስ መኪና ፥ ተርፎ በባንክ የሚቀመጥ ገንዘብ ፥ ወለል ብሎ ይታየናል። ራሰ በራው ትዝ የሚለው ጠጉር ነው። አቅሙ ካለው ጠጉር የሚያበቅል መድኃኒትና ሐኪም ያፈላልጋል። የረገፈ ጠጉሩ የተመለጠ ራሱ ሁሌ ያሳስበዋል። ትልቅ ነገር የጐደለበት ፥ ከሰው በታች የሆነ ይመስለዋል። የአፍንጫ ፥ የጥርስ ፥ የከንፈር ነገር የሚያሳስበውም አለ። የቁመቱ ማጠር ወይም መንቀዋለልም የሚያስጨንቀው ብዙ ነው። ባለማግባቱ የሚያማርር ፥ አግብቶም ልጅ ባለመውለዱ መፈጠሩን የሚረግም ብዙ ነው። ለመሆኑ እንደ ጉድለት የቆጠርነው ይህ ሁሉ ቢሟላልን እናመሰግን ይሆን? ባማረ ቤት ተቀምጠው ፥ ዘመናዊ መኪና እየነዱ ፥ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ እየመነዘሩ ፥ መልከ መልካም ተብለው የተደነቁ ፥ በመንፈሳዊውም በሥጋዊውም በእውቀት የመጠቁ ነገረ ግን በሐዘን ተጨብጠው ፥ በእንባ ተነክረው የሚኖሩ ብዙ ናቸው። ከዚህም አልፈው ራሳቸውን እስከ ማጥፋት የደረሱ ጥቂት አይደሉም። እግዚአብሔርን በዓለም መለወጥ ኪሳራ እንጂ ትርፍ የለውምና። ስለሆነም ዓለም ጥላዋን ጥላብን የጠቆርን ፥ መንፈሳዊው መልካችን የጠፋብን ፥ ወደ ዓለም ዞረን የምንጸልይ ፥ ዓለምን የምናመልክ ሁሉ በሥጋ ሳይሆን በነፍስ «ምን ይጐድለናል?» ልንል ይገባናል። የነፍሳችን ከተሟላ የነፍስ በረከት ለሥጋ ይተርፋልና።

images

      አንድ ወጣት ባዕለጸጋ ወደ ጌታችን መጥቶ፦ «ቸር መምህር ሆይ ፥ የዘለዓለምን ሕይወት እወርስ ዘንድ ከበጎ ሥራ ወገን ምን ላድርግ?» አለው። እርሱም፦ «ለምን ቸር ትለኛለህ ? ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ማንም ቸር የለም፤ » አለው። « ቃልም እግዚአብሔር ነበረ ። . . . ያም ቃል ሥጋ ሆነ ፤ ( ከድንግል ማርያም የነሳውን ሥጋና ነፍስ ተዋሕዶ ሰው ሆነ ) ፤ » እንዲል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ነው። ዮሐ ፩ ፥ ፩። ስለሆነም ቸር ነው ፥ ቸር መባልም ይገባዋል። ታዲያ ለምንድን ነው ወጣቱን ባዕለጸጋ « ለምን ቸር ትለኛለህ ?» ያለው ፥ እንል ይሆናል። ጌታችን እንዲህ ማለቱ ስለሁለት ነገር ነው። አንደኛው ፦ « የባህርይ አምላክ መሆኔን ሳታምን ለምን ቸር ትለኛለህ? » ሲለው ነው። ሁለተኛውም ይህ ሰው ውዳሴ ከንቱ ሽቶ (ፈልጐ) በተንኰል የመጣ ሰው ነው። አመጣጡ ፦ « እኔ ቸር ስለው ፥ እርሱም አንተም ቸር ነህ ፤ » ይለኛል ብሎ ነው። ቅዱስ ዳዊት ፦ « እግዚአብሔር ልቡናን እና ኲላሊትን ይመረምራል። » እንዳለ ፥ እርሱ ልብ ያሰበውን ፥ ኲላሊት ያጤሰውን ያውቃል። መዝ ፯ ፥ ፱። ቅዱስ ዮሐንስም ፦ ጌታችን ኢየሱስም በፋሲካ በዓል በኢየሩሳሌም ሳለ ብዙ ሰዎች ያደረገውን ተአምራት ባዩ ጊዜ አመኑ። እርሱ ጌታችን ግን አያምናቸውም ነበር ፥ ሁሉን እያንዳንዱን ያውቀዋልና ። የሰውንም ግብሩን ሊነግሩት አይሻም ፥ እርሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና።» ብሏል። ዮሐ ፪ ፥፳፫ ። ይህን ሰው « ቸር መምህር ሆይ » ፥ ሲል ላየው ፥ ለሰማው ሰው ፍጹም አማኝ ይመስላል። ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ላየን ፥ ለሰማን ሁሉ አማኝ የምንመስል በእርሱ ዘንድ ግን ከምእመናን (ከአማኞች) የማንቆጠር ብዙ ሰዎች አለን። የአምልኮት መልኩ ፥ ቅርጹ እንጂ ይዘቱ የለም። “ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚመርጡ ይሆናሉ። የአምልኮት መልክ አላቸው፥ ኃይሉን ግን ይክዱታል” እንዳለ። /፩ኛ ጢሞ ፫ ፥ ፬/።
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፦ ልባቸውንም አፋቸውንም አንድ አድርገው የሚያምኑትን ምስጋና እንጂ ውስጣዊ እምነት የሌላቸውን ሰዎች መዝሙር ፥ ውዳሴ ፥ ቅዳሴ ፥ እንደማይቀበል ከተናገረ በኋላ ፦ « ወእመሰ ትፈቅድ ትባእ ውስተ ሕይወት ፥ ዕቀብ ትእዛዛተ ፤ ወደ ሕይወት ልትገባ ( የማታልፍ ርስት መንግሥተ ሰማያትን ልትወርስ ) ብትወድድስ ትእዛዛትን ጠብቅ ፤ » ብሎታል። ምክንያቱም ፦ « ሕጉ ቅዱስ ነው ፥ ትእዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናትና » ሮሜ ፯ ፥፲፪። ቅዱስ ዳዊትም ፦ «የእግዚአብሔር ሕግ ንጹሕ ነው ፥ ነፍስንም ይፈውሳል . . . . . የእግዚአብሔር ሥርዓት ቅን ነው ፥ ልብንም ደስ ያሰኛል፤የእግዚአብሔር ትእዛዝ ብሩኅ ነው ፥ ዓይኖችንም ያበራል።» ብሏል።» መዝ ፲፰ ፥ ፰። « ከአእላፋት ወርቅና ብር ይልቅ የአፍህ ሕግ ይሻለኛል።» ያለውም ለዚህ ነው። መዘ ፩፻፲፰ ፥ ፸፪ ።

      ወጣቱ ባዕለጸጋ ሕጉን እንዲያከብር ፥ ትዕዛዙን እንዲጠብቅ በተነገረው ጊዜ ፦ « የትኞቹን?» ሲል ጠየቀ። ጌታም ፦ አትግደል ፥ አታመንዝር ፥ አትስረቅ ፥ በሐሰትም አትመሰክር ፥ አባትህንና እናትህን አክብር ፤ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ አድርገህ ውደድ ።» አለው። ጐልማሳውም ፦ « ይህን ሁሉ ከሕፃንነቴ ጀምሬ ጠብቄያለሁ ፥ እንግዲህ የሚቀረኝ (የሚጐድለኝ) ምንድነው?» በማለት በኲራት ጠየቀ።ይህ ወጣት ከትናንት እስከ ዛሬ (ከሕፃንነት እስከ ወጣትነት) ያለውን ተናገረ እንጂ ነገ ምን እንደሚሆን አያውቀውም። አብዛኛው ሰው ወጣትነት እስከሚጀምረው ድረስ ሕጉን ለማክበር ፥ ትእዛዙን ለመጠበቅ አይቸገርም። የሚቸግረው ወጣትነት ጓዙን ጠቅልሎ ሲመጣ ነው። የወጣትነት ጓዝ ደግሞ ክፉ ምኞት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ጢሞቴዎስን ፦ «ከክፉ የጐልማሳነት ምኞት ግን ሽሽ ፥ በንጹሕም ልብ ጌታን ከሚጠሩ ጋር ጽድቅን እምነትን ፍቅርን ሰላምን አጥብቀህ ተከተል ።» ያለው ለዚህ ነው። ፪ኛ ጢሞ ፪ ፥፳፪ ።

      በተለይም የእሳትነት ዘመን (ወጣትነት) እና ገንዘብ ሲገናኙ ከባድ ነው። የሥጋ ፍላጎት በሚበዛበትና በሚያይልበት በወጣትነት ዘመን እንደልባችን የምናዝዘው ፥ ብዙ ገንዘብ ካለ ካላወቁበት በእሳት ላይ ጭድ ማለት ነው። « እድሜ ለገንዘቤ ፥» ወደ ማለት ገንዘብን ወደ ማምለክ ይኬዳል። እንዲህ ከሆነ ደግሞ በገንዘብ የማይሠራ ኃጢአት ፥ ለገንዘበ ተብሎ የማይፈጸም ወንጀል የለም። ሃይማኖትንም ያስክዳል። ቅዱስ ጳውሎስ « ዳሩ ግን ባለጠጋ ሊሆኑ የሚፈልጉ ፥ በጥፋትና በመፍረስ ፥ ሰዎችን በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙም ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ። ገንዘብን መውደድ (ማምለክ) የክፋት ሁሉ ሥር ነውና ፥ አንዳንዶችም ይህን ሲመኙ ፥ ከሃይማኖት ተሳስተው (ሃይማኖታቸውን ለውጠው) በብዙ ሥቃይ ራሳቸውን ወጉ ። » እንዳለ። ፩ኛ ጢሞ ፮ ፥ ፱። Continue reading

ሰላም ለእናንተ ይሁን!! /ዮሐ 20፥19/

ይህ ቃል የተናገረው ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ሐዋርያት አይሁድን ፈርተው በተዘጋ ቤት ውስጥ እያሉ ፡ ጌታችን በሩ እንደተዘጋ ገብቶ በመካከላቸው ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” በማለት ፈርተው የነበሩትን ሐዋርያት አጽናንቷቸዋል፡፡

images

ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ጸንተው የመንፈስ ቅዱስን ኃይል ከመቀበላቸው በፊት እንደማንኛውም ሰው በሥጋቸው ፈሪዎች ነበሩ፡፡ ጌታችን ከተያዘበት ጸሎተ ሐሙስ ማታ ጀምሮ በከፍተኛ ፍርሃት ውስጥ በመሆን በራቸውን ዘግተው ሳሉ “የሰላም አለቃ” /ኢሳ. 9፥6/ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ብሏቸዋል፡፡

“ለክፉዎች ሰላም የላቸውም” /ኢሳ 48፥22/ እንዲል አይሁድ በክፋታቸው እራሳቸው ሰላም አጥተው የሰላም አለቃ የሆነውን ጌታ በመስቀል ላይ ሰቀሉት። ደቀ መዛሙርቱንም ማሳደድና ማስፈራራት ሥራቸው አደረጉት። ዛሬም በዓለማችን ላይ ለራሳቸው ሰላም አጥተው የሰውን ሰላም የሚያውኩ ብዙ ይገኛሉ። ብዛት ያላቸው ንጹሐን ሰዎች አረጋዊያንና ሕፃናት ሳይቀሩ ለእንግልት ሲዳረጉ ማየት የዚህ ዓለም አንዱ አሳዛኝ ገጽታ ነው። እንዲሁም ከፍርሃት፤ከጭንቅና ከመከራ የተነሣ በራቸውን ዘግተው በሚኖሩ ሰዎች ዓለማችን ተሞልታ ትገኛለች። ጌታችን “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ያላቸው በችግር ውስጥ ላሉ ወገኖቻችን ጭምር ነው፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ በዝግ ቤት ሲገለጥ አብሯቸው ያልነበረው ቶማስ ስለጌታ ትንሣኤ ሲነግሩት አላመነም። የችንካሩን ምልክት በአይኔ ካላየሁ፤ ጣቴንም ወደ ተቸነከረበት ካልጨመርኩ እጄንም ወደ ጎኑ ካላገባሁ አላምንም እስከማለት ደርሷል። ቶማስ የጌታውን ትንሣኤ በደቀ መዛሙርቱ ሲነገረው የተጠራጠረውን ለማመንና ለመቀበል ከብዶታል። በጦር የተወጋ ጎኑን የተቸነከረሩ እጆቹን ካላየሁ አላምንም ስላለ ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ቀድሞ እንደተገለጸው በመካከላቸው ተገኝቶ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው። ቶማስንም ተጠራጣሪ አትሁን ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን ንካ፤ እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ ባለው መሰረት የተቸነከሩ እጆቹን የተወጋ ጎኑን በመንካት ትንሣኤውን አምኖ ተቀብሎል። ጌታዬ አምላኬም” በማለት የክርስቶስን አምላክነትና ጌትነት መስክሯል። ያመነው አይቶና ዳስሶ ስለነበር ብፁዓንስ ሳያዩ የሚያምኑ ናቸው” ብሎታል። በዘመናችን እንደ ቶማስ ለማመን ሳይሆን ለመካድ የሚጠራጠሩ አሉ። እነዚህ ጌታን የሰቀሉትን አይሁድን ይመስላሉ። ብዙ ገቢረ ተአምራቱን ቢያዩም አላመኑበትም። በመስቀል ላይ እንደወንጀለኛ በመስቀል የክፋት ተምሳሌት ሆኑ፡፡

images (1) Continue reading